1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

«የአማራ ሕዝብ በኢትዮጵያ ያልተነገረለት ሥቃይ»

ማክሰኞ፣ ሚያዝያ 22 2016

የአውሮጳ የሕግና ፍትህ ማዕከል፦ ኢትዮጵያ ውስጥ የአማራ ኅብረተሰብ «ብርቱ የሰብአዊ መብት ጥሰት» ይፈጸምበታል በማለት ጥልቅ ምርመራ ያደረገበትን ዘገባ ይፋ አደረገ ። «የአማራ ሕዝብ በኢትዮጵያ ያልተነገረለት ሥቃይ» በሚል ርእስ ይፋ የሆነው ባለ 18 ገጽ ዘገባ ከጅምላ ጭፍጨፋ እስከ ድሮን ጥቃት ደረሰ ያለውን ዘግናኝ ግድያ በዝርዝር አስፍሯል ።

https://p.dw.com/p/4fMSS
በአማራዎች ላይ የሚደርሰው ማሳደድ እና ግድያ ይቁም በሚል ሮም ጣሊያን ውስጥ በኢትዮጵያ መንግስት ላይ የተደረገ ተቃውሞ።
በአማራዎች ላይ የሚደርሰው ማሳደድ እና ግድያ ይቁም በሚል ሮም ጣሊያን ውስጥ እንደ ጎርጎሪዮስ አቆጣጠርር ነሐሴ 2023 በኢትዮጵያ መንግስት ላይ የተደረገ ተቃውሞ። ፎቶ፦ ከማኅደርምስል Marcello Valeri/ZUMA/picture alliance

የአውሮጳ የሕግና ፍትህ ማዕከል፦ ኢትዮጵያ ውስጥ የአማራ ኅብረተሰብ «ብርቱ የሰብአዊ መብት ጥሰት» ይፈጸምበታል በማለት ጥልቅ ምርመራ ያደረገበትን ዘገባ ይፋ አደረገ ። «የአማራ ሕዝብ በኢትዮጵያ ያልተነገረለት ሥቃይ» በሚል ርእስ ይፋ የሆነው ባለ 18 ገጽ ዘገባ ማዕከሉ ከጅምላ ጭፍጨፋ እስከ ድሮን ጥቃት ደረሰ ያለውን ዘግናኝ ግድያ በዝርዝር አስፍሯል ። በዚህ ዘገባ መሠሰረትም ማዕከሉ ለተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) 47ኛው የሰብአዊ መብቶች ምክር ቤት ግምገማ የሚሆን ደብዳቤ ማስገባቱንም ይፋ አድርጓል ። ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብቶች ላይ የሚወያየው የተመድ 47ኛው ጉባኤ በሚቀጥለው ዓመት ከጥቅምት 25 ቀን፣ 2017 ዓ.ም ጀምሮ ለ11 ቀናት ይካሄዳል ።

ተደጋጋሚና ሆን ተብለው የደረሱ የጅምላ ጭፍጨፋዎች

የአውሮጳ የሕግና ፍትህ ማዕከል ዝርዝር ዘገባ፦ ከቡራዩ ጭፍጨፋ አንስቶ እስከ ሻሻመኔ፤ ወለጋ እና መተከል የጅምላ ጭፍጨፋዎች ሰፊ ምርመራ ተደርጎበታል ። የምርመራ ውጤቱም፦ «ብሄር ላይ ያነጣጠረ ጥቃት እና የዘር ማጥፋት (የጄኖሳይድ) አዝማሚያ በኢትዮጵያ» በሚል ርእስ ስር ተብራርቷል ። ማዕከሉ በአማራ ክልል «ሲቪሊያን ላይ የድሮን ጥቃት ስለመፈጸሙ ተደጋጋሚ መረጃዎች አሉ» ብሏል ። «የድሮን ጥቃት ዋነኛ ትኩረት የሚያሻው ጉዳይ ቢሆንም፤ በአማራ ክልል ያለው አሳሳቢ የሰብአዊ መብት ጥሰት ትኩረት ይሻል» ሲልም አክሏል ። ማዕከሉ ከፍርድ ውጪ ይፈጸማሉ ስላላቸው የጅምላ ግድያ እንዲሁም የደቦ እስርም ያጠናቀረውን ዝርዝር ዘገባ ከሰሞኑ ለንባብ አብቅቷል ። እነዚህ ተከታታይ ጥቃቶችም፦ «በሰብአዊነት ላይ የተፈጸሙ ወንጀሎች መመዘኛዎች ብቻ ሳይሆኑ፤ የዘር ማጥፋት (ጄኖሳይድ) ስልታዊ አቅጣጫን ያመላክታሉ»ም ሲል ማዕከሉ አስጠንቅቋል ።

ከግድያ የተረፉት በርካቶች ከቀዬ መንደራቸው ተፈናቅለዋል ።
ከግድያ የተረፉት በርካቶች ከቀዬ መንደራቸው ተፈናቅለዋል ። ፎቶ፦ ከማኅደርምስል Maria Gerth-Niculescu/DW

ግድያና ማፈናቀል

የምርመራ ውጤቱ፦ በክርስቲያኖች ላይ የተፈጸሙ ተከታታይ ጥቃቶችን በተመለከተም በተለይ እንደ ጎርጎሪዮስ አቆጣጠር «በ2018 እና 2019 ባሉት ሁለት ተከታታይ ዓመታት ብቻ ወደ 30 የሚጠጉ አብያተ ክርስቲያናት ላይ በመላ ሀገሪቱ ጥቃት ደርሷል» ሲል ዘግቧል ። ተከታታይ ጥቃቶች እና ክስተቶች በተለይም አማራ የሆኑ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታዮች ላይ ያነጣጠሩ መሆናቸው ስለመመላከቱም ዘገባው ጠቅሷል ። የአውሮጳ የሕግና ፍትህ ማዕከል የቡራዩ ጭፍጨፋን፣ የሻሸመኔን ጭፍጨፋ እንዲሁም በወለጋ እና በመተከል ዞን ዒላማ ተደርገው የተፈጸሙ በርካታ ግድያዎችን ጨምሮ በሀገሪቱ በርካታ ጉልኅ ክስተቶችን መመዝገቡን ገልጿል። ከግድያ እና ጭፍጨፋው ባሻገር፦ የምርመራ ውጤቱ በአማራው ማኅበረሰብ ላይ በተለይም በመዲናዋ ዙሪያ ባሉ አካባቢዎች እየደረሰ ያለውን የግዳጅ መፈናቀል በግልጽ ያሳየ ነው» ሲልም ማዕከሉ ጠቅሷል። «በመንግስት የከተማ ልማት ፕሮጄክቶች ሽፋን የተሰጠው» ያለው ይህ መፈናቀል «ኦሮሞ ያልሆኑትን ባልተመጣጠነ ሁኔታ በመጉዳቱ የብሄር መድሎ ሥጋት ፈጥሯል»ም ብሏል የአውሮጳ የሕግና ፍትህ ማዕከል ዝርዝር ዘገባ ።

የአውሮጳ የሕግና ፍትህ ማዕከል፦ ኢትዮጵያ ውስጥ አማራ ሕዝብ ላይ የሚደርሰው በደል «ሰሚ አልባ» ሆኖ መቆየቱን ገለጸ
የአውሮጳ የሕግና ፍትህ ማዕከል፦ ኢትዮጵያ ውስጥ አማራ ሕዝብ ላይ የሚደርሰው በደል «ሰሚ አልባ» ሆኖ መቆየቱን ገለጸ

የታጠቁ ቡድኖች እና የአካባቢ ባለስልጣናት ሚና

የአውሮጳ የሕግና ፍትህ ማዕከል በዘገባው፦ «የአማራ ሕዝብ በተለይም ባለፉት አምስት ዓመታት ለተደጋጋሚ የጅምላ ጭፍጨፋዎች ተዳርጓል» ብሏል ። ይህ ግድያ፤ ጭፍጨፋ እና በደል የሚቀናጀውም «በታጠቁ ቡድኖች ነው፤ ብዙውን ጊዜም የአካባቢ ባለሥልጣናት ተባባሪ አለያም በቸልታ ጥቃቱን ሲቀበሉ» እንደሚስተዋል ዘገባው ጠቁሟል ። እነዚህ የጅምላ ጭፍጨፋዎችም «በአማራ ማኅበረሰብ ላይ በስፋት ከተነጣጠረው ሆን ተብሎ የሚፈጸም ጥቃት አካል ነው» ሲልም ዘገባው ጠቅሷል ።

የአውሮጳ የሕግና ፍትህ ማዕከል፦ ኢትዮጵያ ውስጥ በአማራ ሕዝብ ላይ ይደርሳል ካለው መጠነ ሰፊ የሰብአዊ መብት ጥሰት አንጻርም «የተመድ ገለልተኛ የመርማሪ ቡድን እንዲቋቋም» ምክረ-ሐሳብ አቅርቧል ። የምርመራ ቡድኑም «ጥቃትና በደሎች ላይ ዝርዝር ማስረጃዎችን እና ሰነዶችን እንዲያሰባስብ፤ ስለተፈጸመው ግፍም ዓለም አቀፍ ማኅበረሰቡን በማሳወቅ ለቀውሱ ምላሽ እንዲሰጥ ተልእኮ ሊሰጠው ይገባል» ሲልም አክሏል ። በተመድ ምርመራ ቡድን ግኝት መሰረትም «ተጠያቂዎች ለፍርድ እንዲቀርቡ» የሚልም ምክረ-ሐሳብ ማዕከሉ በምርመራ ዘገባ ውጤቱ መደምደሚያ ላይ አስፍሯል ። ማዕከሉ ተፈፀመ ሥላለዉ የሰብአዊ መብት ጥሰት የመንግስት ባለሥልጣናትን ሥለማነጋገሩም ሆነ ያገኘዉ መልስ ሥለመኖር አለመኖሩ በዘገባዉ አልጠቀሰም።

ማንተጋፍቶት ስለሺ

ነጋሽ መሐመድ